የእነ እስክንድር ነጋ መዝገብ ለተጨማሪ ክርክር ከጠቅላይ ፍርድ ቤት ወደ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ተመለሰ
ግንቦት 04፤ 2013 - የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ሁለተኛ ወንጀል ችሎት ባለፈው ችሎት የዐቃቤ ሕግ አቤቱታ ላይ መዝገቡን መርምሮ ብይን ለመስጠት በቂ ግዜ ስላላገኘሁ በሚል ተለዋጭ ቀጠሮ መስጠቱ ይታወሳል። በእነ እስክንድር ነጋ መዝገብ እስክንድርን ጨምሮ አስከ አራተኛ ተከሳሾች በጠበቆቻቸው ተወክለው ቀርበዋል።
ዐቃቤ ሕግ ፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የምስክር ሒደቱን በሚመለከት በግልጽ ችሎት እንዲሰማ ውሳኔ ሰጥቶ የነበረውን ውሳኔ ይግባኝ በማለት ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት 16 ምስክሮችን በዝግ ችሎት ቀሪ 5 ምስክሮቹ ደግሞ ከመጋረጃ ጀርባ እንዲሰሙለት መጠየቁ የሚታወስ ነው።
ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በሁለቱም ወገን የተነሱ ሐሳቦችን በመቀበል ነገር ግን ዐቃቤ ሕግ በመስከረም 4፣ 2013 ባስገባው የምስክር ደኅንነት ጥበቃ አቤቱታ ላይ ለምስክሮቹ አስጊ ናቸው ያለውን ጉዳዮች ዘርዝሮ ባለማቅረቡ፣ አሁን ስጋቴ ናቸው ብሎ ያመነባቸውን ጉዳዮች በዝርዝር በማስቀመጥ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክርክር እንዲደረግበት ሲል ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ቀጣዩ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ክርክር ግንቦት 09፣ 2013 እንዲደመጥ ቀጠሮ ተይዞለታል። ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሚያዝያ 15 በዋለው ችሎት የተከራካሪ ወገኖችን መከራከሪያ ነጥቦች ያደመጠ መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል።
Add a review