ካርድ በኢትዮጵያ የምርጫ ሕግጋት ለውጦች ላይ የምክክር መድረክ አዘጋጀ
የመብቶችና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካርድ) በኢትዮጵያ የምርጫ ሕግጋት ለውጦች ዙሪያ ጥር 8፣ 2012 በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባዘጋጀው የምክክር መድረክ የበይነመረብ ጸሐፊዎችን አሳተፈ። የምክክር መድረኩ የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና የምርጫ ሥነ ምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ላይ የተደረገ ሲሆን፥ 24 የተለያዩ ድረገጾች ላይ የሚጽፉ የዲጂታል ይዘት አቅራቢዎች እንዲሳተፉበት ተደርጓል። የምክክር መድረጉ ላይ የባለሙያ ገለጻ ያደረጉት የሕግ ማሻሻያ ግብረ ኀይል አባል እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የኮሙኒኬሽን አማካሪ ሶልያና ሽመልስ ሲሆኑ፥ ከበይነመረብ ይዘት አቅራቢዎቹ ጋር የጥያቄና መልስ ጊዜም ነበራቸው።
የምክክር መድረኩ ዓላማ በሕግጋት ለውጦቹ ላይ ግንዛቤ ማስጨበጥ እና የኢንተርኔት ላይ ጸሐፊዎች ስለ ሕጋዊ ለውጦቹ እና ቀጣይ ሁኔታዎች መወያየት የሚችሉበትን መድረክ መፍጠር ነበር።
የምክክር መድረኩ በፍሪደም ሀውስ ደጋፊነት የተዘጋጀ ሲሆን፣ የካርድ የፕሮግራም ዳይሬክተር አጥናፉ ብርሃኔ የበይነመረብ ላይ ይዘት አቅራቢዎቹ አዋጆች በሚወጡበት እና በሚከለሱበት ጊዜ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲጫወቱ ጥሪ አቅርበዋል። ካርድ ከምክክር መድረኩ ባሻገር የማኅበራዊ ሚዲያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ያካሔደ ሲሆን፣ አዲሱን የምርጫ ሕግ ለጋዜጠኞች ማጣቀሻ በሚሆን መልኩ አዘጋጅቶ በሶፍት እና ሀርድ ኮፒ በማዘጋጀት ለሚመለከተው አካላት እንዲደርስ አድርጓል።
የማጣቀሻውን ቅጂ እዚህ ክሊክ በማድረግ ዳውንሎድ ያድርጉ።
Add a review